በፋሲል አረጋይ
የተጠቀሰው መረጃ
ቲክቶክ ፣ ፌስቡክንና ኤክስን ጨምሮ በተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎች ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) በአፋር ክልል ተኩስ እንደጀመረ / የተኩስ ልውውጥ እንደነበረ “ያሳያል” በሚል አንድ ቪዲዮ ስለ ግጭቱ ከሚያብራሩ ጽሁፎች ጋር ተሰራጭቷል።
ብያኔ
ቪዲዮው ከቀረበው መረጃ ጋር ግንኙነት የሌለው በመሆኑ MFC ሀሰት ሲል በይኖታል።
የማጣራት ስራ እና ግኝቶቹ
“ህወሓት በአፋር ተኩስ ጀመረ” በሚል አንድ ቪዲዮ በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ በስፋት ተሰራጭቷል፡፡ ከነዚህ መካከል በቲክቶክ የተሰራጨውና በህዳር 2/2018 ዓም የተለጠፈው ቪዲዮ ከአንድ ሚሊየን በላይ ዕይታ ያገኘ ሲሆን፤ ይህ ዘገባ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ከሶስት ሺህ በላይ ሰዎች አጋርተውታል (አርካይቭ እዚህ ይመልከቱ)።
ከዚህም በተጨማሪ ቪዲዮው በተለያዩ የፌስቡክ ገጾች ላይ ተሰራጭቶ በሺዎች እይታዎችን ማግኘት የቻለ (ይህንን ፣ ይህንን እና ይህንን ማስፈንጠሪያ ይመልከቱ ) ሲሆን በኤክስ ማህበራዊ ሚዲያ ላይም በህዳር 3/2018 ዓም መለጠፉን ተመልክተናል፡፡ (እዚህ ይመልከቱ)

MFC በምረመራ ሂደቱ Invid እና Google Lens የተባሉ የምስል ይዘት ማጣሪያ ዲጂታል መሳሪያዎችን የተጠቀመ ሲሆን በመረጃው ላይ እንደተገለጸው ቪዲዮው “ህወሓት በአፋር ተኩስ እንደጀመረ” የሚያሳይ አይደለም። ማሳያዎችም፦
ማሳያ 1፤ የጊዜው ትክክለኝነት ምርመራ
ቪዲዮው የተለጠፈው ጥቅምት 26 ፣ 2018 (November 5, 2025) ነው። ሆኖም ተመሳሳይ ቪዲዮ መስከረም 14 ቀን 2018 በቲክቶክ እንደተለቀቀ ያሳያል (እዚህ ይመልከቱ)። በዚህም ህወሓት በአፋር ተኩስ እንደጀመረ ከተጠቀሰው መረጃ በፊት ቪዲዮው ኢንተርኔት ላይ የሚገኝ በመሆኑ ወቅታዊ አይደለም።
ማሳያ 2፤ የመረጃው ኦሪጂናልነት
በቪዲዮው ላይ የሚሰማው የተኩስ ድምጽ እውነት እንዲመስል ታስቦበትና የተመልካችን አመኔታ ለማግኘት በሚል ተዛብቶ/ተቀናብሮ የቀረበ ነው። ምንም እንኳን ከላይ በተገለጸውና ለመጀመሪያ ጊዜ በተጋራው ቪዲዮ ላይ ጭምር ይሄው ድምጽ ጥቅም ላይ የዋለ ቢሆንም ድምጹ የተወሰደው ከአምስት ወራት በፊት (May 28, 2024) ቲክቶክ ላይ ከሚገኝ ቪዲዮ ነው። በተጨማሪም ይሄንኑ ድምጽ በመጠቀም የተሰሩ ከ9ሺህ በላይ ቪዲዮዎች በቲክቶክ ላይ ብቻ ይገኛሉ። (እዚህ ይመልከቱ)
መደምደሚያ
ከአንድ ሚሊየን በላይ ዕይታ ያገኘውና “ህወሓት በአፋር ተኩስ ከፈተ” ከሚል ጽሁፍ ጋር የተሰራጨው ቪዲዮ የተጠቀሰውን መረጃ የማያሳይ በመሆኑ MFC ሀሰት ሲል በይኖታል።
አውድ
የአፋር ብሔራዊ ክልል መንግስት ጥቅምት 26 ቀን 2018 ባወጣው መግለጫ የ”ህወሓት ቡድን” ሲል የገለጸው ቡድን ወደ ክልሉ ወሰን እንደገባና 6 መንደሮችን እንደተቆጣጠረ አስታውቋል። በአፋር ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት የፌስቡክ ገጽ በኩል የተላለፈው ይሄው መግለጫ በክልሉ ዋራዒ እና ሚልኪ በሚባሉ ልዩ አካባቢዎች ምሽት አንድ ሰዓት ላይ በአርብቶ አደሮች ላይ ከባድ መሳሪያ እንደተተኮሰባቸው ይገልጻል። መግለጫው ለዚህ ድርጊት ህወሓትን በመወንጀል የፕሪቶሪያ ስምምነትን አፍርሷል በማለት ተጠያቂ አድርጓል። (መግለጫው እዚህ ይመልከቱ)
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር በበኩሉ የክልሉ ቡድን “ወደ አፋር ክልል ወሰን ዘለቀው በመግባት ጥቃት ፈጽመዋል” መባሉን አስተባብሏል። ጊዜያዊ አስተዳደሩ በክልሉ ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት በኩል ጥቅምት 27 ቀን 2018 የአፋር ክልል መግለጫን በመቃወም ምላሽ ሰጥቷል። በምላሹም “ሰላማዊ እና ፖለቲካዊ ሂደቶችን የሚያውኩ” እና “የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት የሚጎዱ” ያላቸውን “እንቅስቃሴዎች” እየተመለከተ መሆኑን ገልጾ ትግራይ ክልልን ሆን ተብሎ “ለመበጥበጥ” እና “እርስ በእርስ ለማዳማት”፤ በአፋር ክልል ታጣቂዎችን “በማደራጀት፣ እንዲታጠቁ ምቹ ቦታ በመፍጠር እና ተልዕኮ በመስጠት እንቅስቃሴ እየተደረገ ቆይቷል” ሲልም ወንጅሏል። በአፋር ክልል በኩል ታጣቂዎች ካለፈው ዓመት ወዲህ ተደጋጋሚ “ትንኮሳዎች” ሲፈጽሙ መቆየታቸውን በመግለጽ ከስሷል። (መግለጫውን እዚህ ይመልከቱ)
በተጨማሪም የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር መግለጫ ካወጣ ከአንድ ቀን በኋላ ማለትም ጥቅምት 28 ቀን 2018 ህወሓት በሰጠው መግለጫ የትግራይ ክልል ከአፋር ጋር በሚዋስንበት አካባቢ የኢትዮጵያ ፌደራል መንግስት የድሮን ጥቃት በመፈጸም በትግራይ ታጣቂ ኃይሎች ላይ ጉዳት ማድረሱን ገልጿል። (መግለጫውን እዚህ ይመልከቱ)
