በፋሲል አረጋይ
የተጠቀሰው መረጃ
አንዳፍታ የተባለ የፌስቡክ ገጽ “ህወሃት በራያ ዓዘቦ ተኩስ ከፈተ” የሚል መረጃ የጦር መሳሪያ የያዙ ወታደሮችን ከሚያሳይ ምስል ጋር በማያያዝ ለጥፏል።
ብያኔ
ከልጥፉ ጋር የተሰራጨው ምስል አሳሳች ሲሆን ምስሉም በፌደራል መንግስት እና ትግራይ ኃይሎች ጦርነት ወቅት ከነበረ ሁነት የተወሰደ እንጂ የተጠቀሰውን መረጃ የሚያሳይ አይደለም።
የማጣራት ስራ እና ግኝቶች
445 ሺህ ተከታዮች ያሉት “Andafta” የተባለ የፌስቡክ ገጽ ጥቅምት 23 ቀን 2018 “ሰበር – ህወሃት በራያ ዓዘቦ ተኩስ ከፈተ” የሚል መረጃ የትግራይ ክልል አርማ ያለበት ደንብ ልብስ የለበሱ እንዲሁም የጦር መሳሪያ የታጠቁ ወታደሮች ከሚታዩበት ምስል ጋር ለጥፏል። (እዚህ ይመልከቱ)

MultiFact Check (MFC) በፌስቡክ ገጹ ከተሰራጨው መረጃ ጋር ተያይዞ የቀረበው ምስል በራያ ዓዘቦ ተደረገ የተባለውን ተኩስ የሚያሳይ ነው? የሚል መነሻ በመያዝ የማጣራት ስራ ሰርቷል።
የጉግል ሌንስ ምስል ማጣሪያን በመጠቀም በተደረገ የመጀመሪያ ደረጃ የማጣራት ስራ “ህወሃት በራያ ዓዘቦ ተኩስ ከፈተ” በሚል የቀረበው ምስል ከዚህ በፊት በሰሜን ኢትዮጵያ የፌደራል መንግስትና የትግራይ ክልል ኃይሎችን አለመግባባት ብሎም ግጭት በተመለከተ በሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ለተሰሩ ዘገባዎች በግብዓትነት ጥቅም ላይ መዋሉን አረጋግጧል። (ለምሳሌ እዚህ ፣ እዚህ እና እዚህ ይመልከቱ)
በተጨማሪም ይሄው ምስል በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በተለያየ ጊዜ ለሚተላለፉ ሐሰተኛ መረጃዎች በማሳያነት ጥቅም ላይ ሲውል መቆየቱንም MFC ተመልክቷል። (ለምሳሌ እዚህ ይመልከቱ)
በመሆኑም ከላይ እንደተገለጸው የጉግል ሌንስ ምስል ማጣሪያ ምስሉ በልጥፉ ላይ ከቀረበው መረጃ ጋር የሚገናኝ አለመሆኑን አሳይቷል።
በዚህ የማጣራት ሂደት ምስሉ ታህሳስ 11 ቀን 2013 በBBC ዋናው የዜና ገጽ ላይ መለጠፉንም አረጋግጧል። ይሄው ዘገባም ምስሉ በፌደራል ኃይሎች የማጥቃት እርምጃ ወቅት ከመቀሌ ከተማ ለቀው የሚወጡ የህወሃት ታጣቂ ኃይሎችን የሚያሳይ እንደሆነ ገልጿል። (እዚህ ይመልከቱ)

መደምደሚያ
አንዳፍታ የተባለው የፌስቡክ ገጽ የተጠቀመው ምስል ከተገለጸው መረጃ ጋር የማይገናኝ በመሆኑና ይሄንንም የሚያሳይ የጽሑፍ መግለጫ ለመረጃው ተደራሲዎች ባለማስፈሩ MFC አሳሳች ሲል በይኖታል።
ሐሰተኛ እና የተዛቡ መረጃዎችን ለመከላከል በመሰረታዊነት ዜና የሚያስተላልፉ የመደበኛና ዲጂታል መገናኛ ብዙሃን ለመረጃቸው አባሪ አድርገው የሚጠቀሟቸውን ምስሎች ባለቤት ወይም ምንጭ የማሳወቅ እንዲሁም የመግለጫ ጽሁፍ የማስቀመጥ ሙያዊ ኃላፊነት አለባቸው።
አውድ
በትግራይ ክልል ደቡባዊ ክፍል የሚገኘው ራያ ዓዘቦ በኢትዮጵያ ውስብስብ የፖለቲካ ምህዳር ውስጥ የቀውስ ብልጭታ ስፍራ ሆኖ ቆይቷል። በ2013 መጨረሻ እና በ2014 መጀመሪያ ላይ ህወሀት የአማራ እና አፋር ክልሎችን ሲይዝ የራያ ዓዘቦ አዋሳኝ አካባቢዎችን ጨምሮ በርካታ ጥቃቶች እንደነበሩ መረጃዎች ያመለክታሉ።
በ2013 የመንግስት ግንኙነት ያለው የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት (ኢዜአ) እና እንደ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ያሉ ሌሎች ከመንግስት ጋር የተቆራኙ ሚዲያዎች ህዝባዊ ወያነ ሃርነት ትግራይ (ህወሃት) የፌደራል ጦር ሰራዊት ለቅቆ መውጣቱን ተከትሎ በራያ ዓዘቦ አካባቢ በንጹሃን ላይ ጥቃት ፈጽመዋል በማለት ዘግቧል። ይሁን እንጂ በቅርቡ በአካባቢው እንደገና ህወሃት ጥቃት ፈጽሟል የሚለው ነገር እስካሁን አልተረጋገጠም።
በአንፃሩ የትግራይ ጊዜያዊ ክልላዊ መንግስትም በየጊዜው ከአፋር ክልል የሚነሱ ታጣቂዎች በራያ ዓዘቦ አካባቢ ሰላማዊ ዜጎችን እየጨፈጨፉ ነው ሲል በመክሰሱ ዘገባውን የበለጠ ውስብስብ አድርጎታል።
እነዚህ እርስ በርስ የሚጋጩ ዘገባዎች የክልሉን ተለዋዋጭ ባህሪ እና የተሳሳቱ መረጃዎች በቀላሉ ሊሰራጭ የሚችልበትን ሁኔታ ያንፀባርቃሉ። ውጥረቱ እየጨመረ ሲሄድ፣ ኃላፊነት የተሞላበት ዘገባ ለማቅረብ እና በመረጃ የተደገፈ መገለጫዎቸን ለማግኘት የሚደረገው ጥረት ይበልጥ አስፈላጊ ይሆናል።
