በፋሲል አረጋይ
የተጠቀሰው መረጃ፡ አርቲስት ደበበ እሸቱ በ 2013 ዓ/ም የትግራይ ጦርነት ወቅት “ጅብ ከሚበላህ በልተህ ተቀደስ” በማለት በትግራይ ህዝብ ላይ ጥላቻ ሰብኳል
ብያኔ፡ ሐሰት፦ የአርቲስት ደበበ እሸቱ ንግግር የተሰጠው የትግራይ ጦርነት ከመቀስቀሱ በፊት ነው
አርቲስት ደበበ እሸቱ ነሃሴ 11 ቀን 2017 ዓ/ም ከዚህ አለም በሞት መለየቱ ከተሰማ በኋላ አርቲስቱ በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ወቅት በትግራይ ላይ “ጥላቻ ሰብኳል” “ጄኖሳይድ አውጇል” “ጅብ ከሚበላህ በልተህ ተቀደስ” በሚል በትግራይ ላይ የጥላቻ ንግግር አድርጓል የሚሉ የማህበራዊ ሚዲያ ልጥፎች በስፋት ንግግሩን ከሚያሳይ ቪድዮ እና ምስል ጋር ተጋርቷል።
በተለይም “Dominant News” የሚባል 38,000 (ሰላሳ ስምንት ሺህ) ተከታዮች ያሉት የፌስቡክ ገጽ ነሃሴ 11 ቀን 2017 ዓ/ም “በትግራይና በኢትዮጵያ በተደረገው ጦርነት በትግራይ ህዝብ ላይ ጥላቻ ሲሰብክ የነበረው…” እንዲሁም “ጅብ ከሚበላህ ጅብ በልተህ ተቀደስ” የሚለውን የአርቲስት ደበበ እሸቱ ንግግርን በመጥቀስ ከዚህ ዓለም በሞት መለየቱን የሚገልጽ መረጃ አጋርቷል። (እዚህ ይመልከቱ)
መረጃው ከሃያ ሺህ ፣ አርባ አራት ሺህ ፣ ሰማንያ አራት ሺህ እንዲሁም አንድ መቶ ሃያ ሺህ በላይ አባላት በሚገኙባቸው 55 የፌስቡክ ግሩፖች ላይ ጭምር ተደራሽ እንዲሆን ተጋርቷል። (እዚህ ፣ እዚህ እና እዚህ ይመልከቱ)
በተጨማሪም ሌላ የፌስቡክ አካውንት የአርቲስቱን ህልፈተ ህይወት ተከትሎ “ አርቲስት ደበበ እሸቱ በ2013 አ.ም ጦርነት ወቅት ጅብ ከሚበላህ በልተኸው ተቀደስ በሚለው ንግግር ብዙ ውግዘትን እያስተናገደ ነው።” የሚል ጽሁፍ አጋርቷል።
በመሆኑም አርቲስት ደበበ እሸቱ “ጅብ ከሚበላህ በልተህ ተቀደስ” በሚል የተናገረው ንግግር መቼ እና የት የተደረገ ነው የሚለውን MFC አጣርቷል።
በትግራይ ጦርነት ወቅት የተደረገ ንግግር ነው?
አርቲስት ደበበ ንግግር ያደረገበት ሃሳብ የተወሰደው ከሶደሬ ቲቪ ጋር ካደረገው የቪዲዮ ቃለ መጠይቅ መሆኑን በቪዲዮው ላይ ከሚታየው የሶደሬ ቲቪ ማይክራፎኑ በቀላሉ መመልከት ይቻላል። በዚህም ቃለ መጠይቁ የተደረገው መቼ ነው? የሚለውንና የቃለ መጠይቁን አውድ ለመረዳት MFC የሶደሬ ቲቪ ማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ ምርመራ አድርጓል።
በዚህም ቪዲዮው ለመጀመሪያ ጊዜ በሶደሬ ቲቪ የዩቲውብ ገጽ ላይ የተለቀቀው ከሰባት ዓመት በፊት ሰኔ 20 ቀን 2010 ዓ/ም ነው። በቪዲዮው ላይም ቃለ መጠይቁ ሲጀምር ጋዜጠኛው “የተገናኘነው ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በሰኔ 16 ጥቃት የደረሰባቸውን ልትጠይቅ መጥተህ ነው” ሲል አርቲስት ደበበ እሸቱ ደግሞ “አዎ” በማለት ምላሽ ሲሰጥ ይታያል። (እዚህ ይመልከቱ)
በመሆኑም ቪዲዮ ለመጀመሪያ ጊዜ በዩቲውብ ላይ የተለቀቀበትን ጊዜ እና የቃለ መጠይቁን አውድ በመመልከት በፌስቡክ ልጥፉ እንደተገለጸው አርቲስት ደበበ እሸቱ “በትግራይ እና ኢትዮጵያ ጦርነት ወቅት” እና “በ 2013 ዓ/ም ጦርነት ወቅት” ተናግሮታል የተባለው ንግግር የተሳሳተ መሆኑን MFC አረጋግጧል።
አውድ
ሰኔ 16 ፣ 2010 አዲስ አበባ
በቪዲዮው ላይ እንደሚታየው አርቲስት ደበበ እሸቱ የሰኔ 16 ተጎጂዎችን ለመጎብኘት ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል እንደተገኘ ይገልጻል። ሰኔ 16 ቀን 2010 ምንድነው የተፈጠረው?
ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ/ም በአዲስ አበባ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ (ዶ/ር) የድጋፍ ሰልፍ በተካሄደበት ወቅት የቦንም ጥቃት ደርሶ ሁለት ሰዎች ሞተዋል። በመቶዎች የሚገመቱ ሰዎች ለአካል ጉዳት ተዳርገዋል።
አርቲስት ደበበ እሸቱ
አርቲስት ደበበ እሸቱ ተዋናይ ፣ ተርጓሚ ፣ አዘጋጅ ፣ ጋዜጠኛ እና ፖለቲከኛ ነበር። በኪነ ጥበብ ሙያው ከ40 በላይ ተውኔቶች ላይ የተሳተፈ ሲሆን፣ በፊልም ሥራው ውስጥ በኢትዮጵያውያን የተዘጋጁትን ጨምሮ ከአገር ውጪ በሚገኙ ባለሙያዎች የተደረሱ እና ዳይሬክት በተደረጉ ፊልሞች ላይ ተሳትፏል። ከእነዚህም መካከል “ Shaft in Africa” እና “The African Spy” ፊልሞች ይገኙበታል።
አርቲስት ደበበ እሸቱ በ1995 ቀስተደመና ፓርቲን በመቀላቀል የፖለቲካ ተሳትፎውን የጀመረ ሲሆን በ1997 ዓ/ም ተካሂዶ በነበረው ምርጫ የቅንጅት ለአንድነት እና ዲሞክራሲ ፓርቲ አባል በመሆነ በነበረው የፖለቲካ ተሳትፎውም በጉልህ ይታወቃል።
በ1934 ዓ.ም. አዲስ አበባ ውስጥ የተወለደው ደበበ እሸቱ በ 83 ዓመቱ ባሳለፍነው ነሃሴ 11 ቀን 2017 ዓ/ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል። ስርዓተ ቀብሩ ነሃሴ 13 ቀን 2017 ዓ/ም በ 4 ኪሎ መንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡
