በፋሲል አረጋይ
የተጠቀሰው መረጃ
በቅርቡ በማህበራዊ ሚዲያ በተለይም በፌስቡክ ገጾች ላይ አንድ ዘመናዊ የጦር መሳሪያ የሚያሳይ ምስል “በፋኖ የተማረከ ነው” ተብሎ በስፋት እየተሰራጨ ይገኛል።
ብያኔ
ምስሉ አሁን ካለው ወቅታዊ የክልሉ ሁኔታ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት የሌለውና ለረጅም ዓመታት በኢንተርኔት ላይ የነበረ መሆኑን MFC በማረጋገጡ መረጃውን ሐሰት በማለት በይኖታል።
“Ghion Tube” የተባለ የፌስቡክ ገጽ በአማርኛ እንዲሁም “ባራኺ ወዲ ኣሌ” የተባለ ሌላ ገጽ በትግርኛ ቋንቋ ምስሉን በማጋራት “ይህ ውድ መሳሪያ በፋኖ ገቢ ሆኗል ፥ መሳሪያው ከሰሞኑ የተማረከ” የሚል መረጃ አስተላልፈዋል። መረጃውም በወቅታዊው የአማራ ክልል ግጭት ፋኖ ድል እየተቀዳጀ መሆኑን ለማሳየት ታስቦ የቀረበ ነው። (የተጠቀሱትን መረጃዎች ከማህደር እዚህ እና እዚህ ይመልከቱ)

የማጣራት ስራ እና ግኝቶቹ
MultiFactCheck (MFC) የመረጃውን ትክክለኛነት ለማረጋገጥ የምልሰት ምስል ፍለጋ መሳሪያ የሆነውን ጉግል ሌንስ (Google Lens) ተጠቅሟል። በምርመራ ሂደቱም የሚከተለው ውጤት ተገኝቷል።
ምስሉ በመረጃው ላይ እንደተጠቀሰው “በፋኖ ከሰሞኑ የተማረከ” ሳይሆን ከሰባት ዓመታት በፊት ጀምሮ በተለያዩ የማህበራዊ ሚዲያ ገጾች ላይ ሲዘዋወር የነበረ ነው። ለምሳሌ መጋቢት 30 ቀን 2011 ዓ/ም (April 8, 2019 G.C) “Amhara Association of California” የተባለ ገጽ የጦር መሳሪያው ከኦነግ የተማረከ እንደሆነ በመግለጽ ምስሉን ለሌላ ዓላማ ተጠቅሞታል (እዚህ ይመልከቱ)። በተጨማሪም ሌላ የፌስቡክ ገጽ አስቀድሞ ይሄንኑ ምስል መለጠፉም ተረጋግጧል (እዚህ ይመልከቱ)።

አውድ
በአማራ ክልል ያለው የጸጥታ ችግርና ግጭት መነሻው ብዙ ቢሆንም፣ ዋነኛው የፌደራል መንግስቱ የክልል ልዩ ኃይሎችን መልሶ ለማደራጀትና ወደ ፌደራል ፖሊስ ወይም መከላከያ ሰራዊት እንዲቀላቀሉ የወሰነውን ውሳኔ ተከትሎ የፋኖ ታጣቂዎችና የልዩ ኃይሉ አባላት ውሳኔውን በመቃወም ወደ ትጥቅ ትግል በመግባታቸው ነው።
ለሁለት አመት የዘለቀው ግጭት መጠነ ሰፊ ውድመት አስከትሏል። በዚህም በመንግስት ወታደሮችና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል በሚደረጉ ውጊያዎች በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ህይወት ጠፍቷል ፣ የጤና ተቋማት፣ ትምህርት ቤቶችና የመንግስት መሠረተ ልማቶች ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሷል እንዲሁም ግጭቱ በተስፋፋባቸው አካባቢዎች ንጹሃን ዜጎች ለሞት፣ ለእስራትና ለከፍተኛ ስነ ልቦናዊ ጫና ተጋልጠዋል።
በተለይም ከሰሞኑ በደቡብ ጎንደር ደብረ ታቦር ከተማ ላይ በፋኖ ታጣቂዎች እና በመንግሥት ኃይሎች መካከል በተካሄደ ግጭት ፖሊስ ጣቢያዎች እና የመንግሥት ተቋማት እንደተቃጠሉ ፣ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች እና የፋኖ ታጣቂዎች መሞታቸው እንዲሁም በተለያዩ የከተማዋ አካባቢዎች የድሮን ጥቃቶች መፈፀሙ ተዘግቧል።
መደምደሚያ
በመሆኑም “መሳሪያው ከሰሞኑ በፋኖ የተማረከ ነው” ተብሎ የቀረበው መረጃ ሐሰት ነው። ምስሉ የቆየና አሁን በክልሉ ካለው ተጨባጭ ሁኔታ ጋር የማይገናኝ፣ ህዝብን ለማሳሳት የቀረበ መረጃ እንደሆነ MFC አረጋግጧል።
በመረጃው ጥቅም ላይ የዋለው ምስል Maschinengewehr 42 (MG 42) መትረየስን የሚያሳይ ሲሆን ለመጀመሪያ ጊዜ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት በጀርመን እንደተመረተ መረጃዎች ያሳያሉ። በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ጨምሮ የብዙ ሀገራት ጦር ሰራዊት በስፋት ይጠቀምበታል።
