በፋሲል አረጋይ
የተጠቀሰው መረጃ
በጎንደር የሚገኙ የፋኖ ታጣቂዎች የጦር መሳሪያዎችን መማረካቸውን የሚገልጽ መረጃ የተለያዩ ጦር መሳሪዎች ከሚታዩበት የፎቶ መረጃ ጋር በፌስቡክ እና “X” ማህበራዊ ሚዲያ ገጾች ተሰራጭቷል።
ብያኔ
የፎቶ መረጃው የቆየና አሁን ላይ በፋኖ ታጣቂዎች የተማረከ የጦር መሳሪያን የማያሳይ በመሆኑ MFC ሐሰት ሲል በይኖታል።
የማጣራት ስራ እና ግኝቶቹ
በፌስቡክ እና “X” ማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ የሚገኙ ከፍተኛ ተከታይ ያላቸው ገጾች በጎንደር “ፋኖዎች” በጥቂት ሰዓታት ውስጥ መሳሪያዎችን ማረኩ ከሚል መረጃ ጋር አንድ ፎቶ አሰራጭተዋል።
“Ethiopian DJ የኢትዮጵያ ሙዚቃ” የሚል ስያሜ ያለው 189ሺህ ተከታዮች ያሉት የፌስቡክ ገጽ “በአንድ ሰዓት ውጊያ ብቻ በአብርሃጅራ የተማረከ የመሳሪያ ብዛት ነው…ብልጽግና ቲክቶክሮችን እየማረከ ነው” በማለት ምስሉን አጋርቷል። በሌላ በኩል፣ ከ29ሺህ በላይ ተከታዮች ያሉት “Dagmawi M. Belay” የተባለ ገጽ “እጅግ አስደናቂ ድል ፋኖ በጎንደር አስመዝግቧል…በጥቂት ሰአታት ውጊያ የጠላት ሰራዊትን ደምስሶ የማረከው መሳሪያ ነው” በማለት ተመሳሳይ ምስል ለጥፏል። (አርካይቭ የተደረገው መረጃ እዚህ እና እዚህ ይገኛል)

በማህበራዊ ሚዲያ ገጾቹ እንደተገለጸው ምስሉ የፋኖ ታጣቂዎች በጎንደር ከተማ የማረኩትን የጦር መሳሪያ ያሳያል? የሚል መነሻ በመያዝ MultiFactCheck (MFC) የማጣራት ስራ ሰርቷል። በዚህም የማጣራት ሂደት መረጃው ከላይ ከተገለጹት የፌስቡክ እና ኤክስ (X) ገጾች በተጨማሪ ሌሎች ገጾች ላይ ተጋርቷል። (እዚህ ፣ እዚህ እና እዚህ ይመልከቱ)
የማህበራዊ ሚዲያ ገጾቹ የጦር መሳሪያዎቹ መቼ እንደተማረኩ አልገለጹም። ሆኖም “…ብልጽግናም ቲክቶከሮችን መማረኩን ቀጥሏል” የሚል ሀረግ ተጠቅመዋል። ይሄም መንግስት ከማህበረሰብ ባህል የሚጻረር አልባሳት ለብሰዋል በሚል ክስ የቲክቶክ ይዘት ፈጣሪዎችን በቁጥጥር ስር ባዋለበት ወቅት “የተማረከ” ነው የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል።
MFC የጉግል ሌንስ Google Lens ምስል ማሰሻን በመጠቀም ባካሄደው ማጣራት ምስሉ ነሃሴ 5 እና 6 ቀን 2016 ዓ/ም በተለያዩ የፌስቡክ ገጾች ጥቅም ላይ ውሎ እንደነበር አረጋግጧል (እዚህ ፣ እዚህ እና እዚህ ይመልከቱ)። በመሆኑም ታህሳስ 2 እና 3 ቀን 2018 በፌስቡክ እና ኤክስ (X) ገጾች በጎንደር የፋኖ ታጣቂዎች በአንድ ሰዓት ውጊያ የማረኩት የጦር መሳሪያን ያሳያል በሚል የቀረበው ምስል አሁናዊ አለመሆኑን በማረጋገርጥ MFC መረጃውን ሐሰት ሲል በይኖታል።
አውድ
በፌደራል መንግስት ኃይሎች እና በአማራ ክልል የጦር መሳሪያ ታጥቀው በሚንቀሳቀሱ “የፋኖ” ቡድኖች መካከል ግጭት የተቀሰቀሰው ሚያዚያ 2015 ላይ ነበር። በክልሉ የተቀሰቀሰው ደም አፋሳሽ ግጭት ንጹሃንን ለሞት እና አካል ጉዳት ሲዳርግ መጠነ ሰፊ የመሠረተ ልማት ውድመት አድርሷል።
የአማራ ክልላዊ መንግስት በክልሉ ከሚገኙ ታጣቂዎች መካከል በማስረሻ ሰጤ ከሚመራውና ራሱን የአማራ ፋኖ ህዝባዊ ድርጅት ብሎ ከሚጠራው ቡድን ጋር ታህሳስ 4 ቀን 2018 ዓ/ም ስምምነት እንደፈጸመ ተዘግቧል (እዚህ ይመልከቱ)። ሆኖም በክልሉ በፋኖ ስም በሸዋ ፣ ጎጃም ፣ ጎንደር እና ወሎ የሚንቀሳቀሱ በርካታ አንጃዎች አሉ። የአማራ ክልላዊ መንግስት ከእነዚህ ታጣቂ ቡድኖች ጋር ያለው እጣ ፈንታ እስካሁን አልታወቀም።
መደምደሚያ
የፋኖ ታጣቂዎች በዚህ ሰሞን – በጎንደር ፤ ከፍተኛ የጦር መሳሪያ እንደማረኩ የሚያሳይው እና በፍጥነት እየተሰራጨ የሚገኘው ምስል የተሳሳተ ነው። የኋልዮሽ የምስል ፍለጋ መሳሪያዎችን (Reverse Image Search tools) በመጠቀም ያደረግነው ምርመራ እንደሚያሳየው ፤ ምስሉ ቢያንስ ከ2016 ጀምሮ በኢንተርኔት እየተዘዋወረ የቆየ ሲሆን ፤ ይህም በወቅቱ ካለው ግጭት በፊት የሆነ ነው።
የማህበራዊ ሚዲያ ልጥፎች ከአስር አመት ገደማ በፊት የተነሱ የፎቶ ምስሎችንና የተመዘገቡ ክስተቶችን መላልሶ እንደ አዲስ ከትክክለኛው አውድ በተለየ መልኩ በመጠቀም አሳሳይች ይዘትን አሰራጭተዋል። ይህ የMFC ምርመራ፣ የሀሰተኛ መረጃ ፍብረካዎች በአገሪቱ ውስጥ በሚከሰቱ የእርስ በእርስ ግጭቶች ወቅት የህዝብን ስሜታዊ ምላሽ ለማግኘት ታልመው እንደሚሰራጩ ያሳያል።
ይህ ውስን ይዘትም ፣ በምስሉ ላይ የሚታዩት የጦር መሳሪያዎች በቅርብ ጊዜ በጎንደር ዞን ከተደረጉት ውጊያዎች ጋር ምንም ትይይዝ የላቸውም። በዚህም ምክንያት፣ “ይህ ፎቶ በጎንደር ውስጥ የፋኖ ኃይሎች የአሁኑን ድል ያሳያል” የሚለው ይዘት ሀሰተኛ ነው። ይህ የቆዩ ምስሎችን እንደ አዲስ በመጠቀም ወታደራዊ ስኬት የማስመሰል ተግባር፣ ህዝቡን ለማደናገር የሚያገለግል የተለመደ የሐሰት መረጃ ዘዴ ነው። ስለዚህ፣ MFC ከየተጠቀሰው መረጃ ጋር የተለጠፈውን ምስል ሐሰት ሲል በይኖታል።
በመጨረሻም፣ MFC ህዝቡ ዲጂታል መረጃዎችን ከማጋራቱ በፊት ስሜታዊ ይዘትን በጥንቃቄ እና በጥልቀት እንዲመረምር ያሳስባል። የተሳሳተ መረጃ በአስቸኳይ ጊዜ እና በስሜታዊ ሁኔታ ውስጥ በስፋት እንደሚሰራጭ ልብ ይሏል።
ይህም ብዙውን ጊዜ ሂሳዊ አስተሳሰባችንን ለማለፍ “ሰበር ዜና” ተብሎ ይገለጻል። የሐሰት ትረካዎችን ስርጭት ለመከላከል ምንጩን ሁልጊዜ እንዲያረጋግጡም MFC ያሳስባል። በተጨማሪም፣ የምስሎችን ታሪክ ለመፈተሽ እንደ Google Lens ወይም TinEye Reverse Image Search ያሉ መሳሪያዎችን ይጠቀሙ። የመረጃውን ምንጭ በማረጋገጥ፣ በሀሰተኛ መረጃዎች ምክንያት ከሚደርሱ ጉዳቶች ራስዎንና ማህበረሰብዎን ይጠብቁ።
